Tuesday, November 12, 2013

እንቅስቃሴውን የጀመሩት ስዊድናዊ ጠበቃ ከኢትዮጵያውና ጋር ውይይት አደረጉEthiopia Zare (ማክሰኞ ኅዳር 3 ቀን 2006 ዓ.ም. Nov. 12, 2013)፦ ባለፈው ቅዳሜ ጥቅምት 23 ቀን 2006 ዓ.ም. (ኖቬምበር 2 ቀን 2013) የኢትዮጵያ ዲሞክራሲያዊ መድረክ በስዊድን የወያኔን መንግሥት በዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት ለማቅረብ የተጀመረውን ክስ መነሻ በማድረግ የክሱን ሂደት ከሚመሩት ከስዊድናዊው ጠበቃ ከስቴላ ያርዴ እና ከሌሎች እንግዶች ጋር በርካታ ኢትዮጵያውያን በተገኙበት ወይይት አደረገ።

ጠበቃ ስቴላ ያርዴ
Ethiopia Zare (ማክሰኞ ኅዳር 3 ቀን 2006 ዓ.ም. Nov. 12, 2013)፦ ባለፈው ቅዳሜ ጥቅምት 23 ቀን 2006 ዓ.ም. (ኖቬምበር 2 ቀን 2013) የኢትዮጵያ ዲሞክራሲያዊ መድረክ በስዊድን የወያኔን መንግሥት በዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት ለማቅረብ የተጀመረውን ክስ መነሻ በማድረግ የክሱን ሂደት ከሚመሩት ከስዊድናዊው ጠበቃ ከስቴላ ያርዴ እና ከሌሎች እንግዶች ጋር በርካታ ኢትዮጵያውያን በተገኙበት ወይይት አደረገ።
ተሰብሳቢው ህዝብ በከፊል
ውይይቱ ከቀኑ 14፡00 ሰዓት የተጀመረ ሲሆን፣ ውይይቱን የከፈቱት የመድረኩ ሊቀመንበር ም/ኢንስፔክተር ሚሊዮን ብሩ ናቸው። ኢንስፔክተር ሚሊዮን በንግግራቸው መክፈቻ ጥሪ የተደረገላቸውን እንግዶችና ተሰብሳቢውን ህዝብ አመስግነው፤ መድረኩ የተቋቋመበት ዓላማ በሀገር ውስጥና በውጪ የሚደረገውን የነፃነት ትግል የተደራጀ መልክ ይዞ የሚጓዝበትን መንገድ ለማመቻቸትና በየጊዜውም ይሄን መሰል ውይይት በማድረግ ትግሉን ለመርዳት መሆኑን ገልጸው፤ የዕለቱም ስብሰባ የዚህ መነሻ እንደሆነ አስታውቀዋል።   
የዕለቱ የፕሮግራሙ መሪ ጋዜጠኛ ወንድማገኝ ጋሹ፤ ወደ መድረኩ ዶ/ር ሙሉዓለም አዳምን የመጀመሪያው ተናጋሪ አድርገው ጋብዘዋል። ዶ/ር ሙሉዓለም የመድረኩን አዘጋጆች አመስግነው በኢትዮጵያ ውስጥ የሚደረገው የሰብዓዊ መብት ጥሰት በአስከፊ ሁኔታ ላይ መውደቁን፣ ሙስናውም እያደር መባባሱን፣ የመንግሥት ባለሥልጣኖች ወደ ውጪ የሚያሸሹት ገንዘብ እየናረ መሄዱን ገልጸዋል።  
እንዲሁም የዘር ፖለቲካ እየተስፋፋ መሄዱን፣ የስለላ መዋቅሩም መጠናከሩንና ህዝቡ መግቢያ መውጫ ማሳጣቱን፣ ከዛም አልፎ በውጪ በስደት የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ድረስ መዝለቁን አስረድተዋል። የወቅቱን የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትርም ንግግር በመጥቀስ በሰላማዊ ሁኔታ የሚደረገው ትግል አስቸጋሪ ሁኔታ ላይ እንደወደቀ አመላክተዋል።
ሁለተኛው ተናጋሪ የመድረክ መሪው ጋዜጠኛ ወንድማገኝ ጋሹ የነበረ ሲሆን፣ ጋዜጠኛ ወንድማገኝ በሀገራችን ያለው የሰብዓዊ መብት ጥሰት፣ የሰው ልጅን የሰውነት ደረጃ ያቃለለ፣ ሙሉ ለሙሉ ያዋረደና መብት የገፈፈ መሆኑን ጠቅሶ፣ ለሃያ ደቂቃ የቆየ ይኽንኑ የሚያሳይ ፊልም አሳይቷል።
ቀጥሎም የተነሱበትን ዓላማ እንዲያስረዱ በጉጉት ይጠበቁ የነበሩት ስዊድናዊው ጠበቃ ስቴላ ያርዴ ንግግር እንዲያደርጉ ተጋብዘዋል። ጠበቃ ስቴላ ያርዴ የስዊድን ቴሌቪዥን ባሳየው ዘጋቢ ፊልም ስሜታቸው እንደተነካ ገልጸው፤ ይሄንን አሰቃቂ ወንጀል የፈጸመውን የወያኔን መንግሥት ለፍርድ ለማቅረብ እንደተነሱ አስረድተዋል።
በፊልሙ ላይ የታዩት የወንጀል ድርጊቶች ለተነሳንበት ክስ አሳማኝ መረጃ ከመሆኑም በላይ፣ በተለይ በእስር ላይ ያሉ ሰዎችን የመድፈርና የማስወለድ ድርጊት ወንጀሉን የሚያከብደው ሲሆን፤ በቅርባችን ባሉት ስዊድናውያን ጋዜጠኖች ላይም የተፈጸመው የሰብዓዊ መብት ጥሰትና በደል ክሱን እንደሚያጠናክርው ገልጸዋል።
ሁኔታውን ሲያብራሩም አሁን ያሉንን መረጃዎች ይዘን ለሚመለከተው አካል አመልክተናል። ወደ ቀጣዩ እርምጃ ለማለፍ የነሱን ውሳኔ መጠበቅ ይኖርብናል። የስዊድን ፖሊስም ለዚህ ጉዳይ ትብብሩን አልነፈገንም ብለዋል።
ከተሰብሳቢው ህዝብም ክሳችሁ ትኩረት ይዞ የተነሳው በኡጋዴን በታየው በደል ብቻ ነው ወይስ በሌሎችም ክልሎች የተፈጸመውን አጠቃሎ ይይዛል? ለተባሉት ሲመልሱ በሌሎች ክልሎች የተፈጸመውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት ድርጊቱን በሚያስረዳ መልክ ማስረጃ አሰባስበን መያዝ የመጀመሪያ ስራችን ይሆናል ብለዋል።
ማስረጃ ልንሰጣችሁ ብንፈልግ በምን መልኩ ማቅረብ እንችላለን? ለተባለው ጥያቄ ደግሞ ሲመልሱ ማስረጃ ለመስጠት በተናጠል እኔን ማግኘት አያስፈልጋችሁም፤ ከተለያየ ሰውና ቦታ የምታገኙትን መረጃ ይሄንን የሚያሰባስብ የመረጃ ቡድን አቋቁማችሁ ቡድኑ መረጃዎችን አጣርቶና አሰባስቦ ቢሰጠን የተሻለ ይሆናል ብለዋል።
በስብሰባው ላይ የተገኙት የአፋር ህዝብ ብሔራዊ ክልል የሰብዓዊ መብት ተወካይ፤ በበኩላቸው በአፋር ህዝብ ላይ ያለው የሰብዓዊ መብት ጥሰት ከሌላው ክልል ባልተናነሰ ሁኔታ እየተፈጸመ እንዳለ ገልጸው፤ በእጃቸው የሚገኘውን መረጃ ለጠበቃ ስቴላ ያርዴ ሰጥተዋል።
የመጨረሻው ተናጋሪ መቶ አለቃ አበረ አዳሙ ሲሆኑ፤ መቶ አለቃ አበረ ድርጅታዊ ዘረኝነት በሚል ርዕስ የተሰብሳቢውን ህዝብ ስሜት የሳበ ንግግር አድርገዋል። በዚሁ ንግግራቸው እንዳብራሩት የኢትዮጵያ መንግሥት የድርጅታዊ ዘረኝነትን አገዛዝ አጥብቆ ለመያዝ የክልልና የፌዴራል ፖሊስን፣ የደህንነት መምሪያውን፣ የመከላከያ ሠራዊቱን፣ የስራ ፈጻሚ ክፍሎች እንዲሁም የገንዘብ ገቢ የሚያስገኙ ተቋማትን በአንድ ዘር በማደራጀት ኃላፊዎች መድቦ ምንም አይነት ቀዳዳ ሳይከፍት ሁሉን ነገር በቁጥጥሩ ስር በማድረግ ድርጅታዊ ዘረኝነቱን ለማጠናከር ችሏል ብለዋል።
በመሆኑም ተቃዋሚ የሆንን ሁሉ ይህንን ድርጅታዊ ዘረኝነት አውቀን ትግላችንን ማጠናከር ይገባናል፤ ለዚህም የሚያገለግለን መተባበርና እርስ በርሳችን መተሳሰር ሲሆን፤ ይህን የአፈና መዋቅርም ማፍረስ የምንችለው በተጠናከረ የአንድነት ትግል ብቻ ነው በማለት ሰፊ ማብራሪያ ሰጥተዋል። የመቶ አለቃ አበረ ንግግር በብዙዎቹ ታዳሚዎች ላይ ለለውጥ የሚያነሳሳ ስሜት ፈጥሮ ነበር።
በመጨረሻም የውይይት መድረኩ ለወደፊትም ከልዩ ልዩ እንግዶች ጋር በዚህ መልክ ወይይቶች እንደሚደረግ ገልጾ፤ ውይይቱ 18፡00 ሰዓት ላይ ተጠናቋል።

No comments:

Post a Comment