Friday, November 29, 2013

የአውሮፓ ህብረት ተወካዮች ከተቃዋሚዎችን ጋር ተወያዩ

ለአውሮፓ፣ ኤዥያ፣ ካሪቢያን፣ፓስፊክና አፍሪካ ጉባኤ አዲስ አበባ የተገኙት የአውሮፓ ህብረት ተወካዮች በቢሮአቸው ከተቃዋሚዎች ጋር ተወያዩ፡፡ ከስፔን፣ ፖርቱጋል፣ ማልታ፣ ፈረንሳይና እንግሊዝ የተወከሉ ልኡካን በኢትዮጵያ ስላላው አጠቃላይ ሁኔታ ላይ ውይይት አድርገዋል፡፡ ከተቃዋሚዎች በኩል ከመድረክ ዶ/ር መረራ ጉዲና፣ ከአንድነት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳና አቶ አስራት ጣሴ፣ ከመኢአድ አቶ አበባው መሀሪ፣ ከሰማያዊ ፓርቲ አቶ ይልቃል ጌትነት እንዲሁም ከኢዴፓ አቶ ልደቱ አያሌውና የፓርቲው ፀሀፊ ተገኝተዋል፡፡ ከተወካዮቹ በኩል የተነሱት ጥያቄዎች የሚከተሉት ናቸው፡- 
1. የፓርቲዎች ቁጥርስ ለምን በዛ?
 2. በህግ አግባብ የተመዘገቡ ስንት ናቸው? 
3. በፕሮግራምና በርዕዮተ ዓለም ልዩነታቸውና ተመሳሳይነታቸው ምን ይመስላል?
 4. የምርጫ ሥርዓታችሁ የትኛው ነው?
 5. በኢትዮጵያ ያሉ የፖለቲካ እስረኞች ቁጥር ስንት ይሆናል?
 6. ተቃዋሚዎች ከህዝብ ጋር ለመገናኘት ምን ዘዴ ትጠቀማላችሁ? በገጠርና በከተማስ ምን ይማስላል?
 7. ከዲያስፖራ ጋር ያላችሁ ግንኙነትስ እንዴት ያለ ነው?
 8. ከሌሎች ሀገራት ፓርቲዎች ጋር ግንኙነት አላችሁ ወይ?
 9. የአውሮፓ ህብረት ምን ማድረግ (ማገዝ) ይችላል?
  ህብረ-ብሄራዊና ክልላዊ ፓርቲዎች የቁጥራችሁ ምጣኔ ከተሰጡት መልሶች የሚከተሉት የዶ/ር ነጋሶ ሀሳብ ይገኙበታል፡- ኢህአዴግና የመሰረተው መንግስት ህገ መንግስቱን በመጣስ መካናቸውን፤ ህገ- መንግስቱን የሚጥሱ ህጎችን ማውጣት ብርቁ እንዳልሆነ፤ የአንድ ፓርቲ አምባገነንነት ጥግ ድረስ ማድረሱን፤ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎችን በውሸት ክስ እያሰሩ ፓርቲዎችን እንደሚያዳክሙ ለምሳሌ አንዱአለም አራጌና በቀለ ገርባ፤ ተቃወሚዎች ልሳን እንዳያሳትሙ እንደሚደረግና እንደሚዘጋባቸው ለምሳሌ የአንድነት ፓርቲዋ ፍኖተ-ነፃነት፤ የቢሮና የአደራሽ ኪራይ መከለልከል፤ የሰላማዊ ሰልፍና ስብሰባ ማድረግ መከልከል፤ ቅስቀሳ ማድረግ መከልከል (ሰዎች፣ የቅስቀሳ መሳሪያዎችና መኪኖች እንደሚታሰሩ)፣ ሁል ጊዜ ያለው ዛቻ፣ ማስፈራሪያ፣ ድብደባ፣ ጠለፋ፣ ማሰቃየት፤ አባላትን ከመሬት፣ ከስራና ከቤታቸው ማፈናቀል፤ በውሸት ተቃዋሚዎችን ከአሸባሪዎች ጋር ማዛመድ፤ የስም ማጥፊያ ፊልሞችን መፈብረክ፤ እንቅስቃሴን መገደብ፤ መንግስት ፍትሃዊ የሆነና በህግ አግባብ የተቀመጠ የፋይናንስ ድጋፍ ማድረግ ሲገባው ያለማድረግ፤ ዜጎችን ዘር ማጥፋት እስኪመስል ድረስ ከይዞታቸው ማፈናቀል፤ ለውይይትና ለድርድር እንቢ ባይ መሆን የሚሉ የኢህአዴግ ባህሪያት ቀርበዋል፡፡ የአውሮፓ ህብረት ምን ማድረግ ይችላል ለሚለው ደግሞ የሚከተሉት ማሳሰቢያዎች ተሰጥተዋል፡- —————————————— ለልማትና ለማህበራዊ ጉዳዮች ድጋፍ አትሥጡ ባይባልም ኢህአዴግ ግን የተሰጠውን ዕርዳታ 1. የራሱን ቢሮክራሲ እንደሚያጠናክርበት 2. አፋኝ የፀጥታና የፖሊስ ኃይሉን እንደሚያጠናክርበት 3. የፓርቲውን መዋቅሮች እንደሚያደራጅበት እንዲያውቁ ተብሏል፡፡ በቅርቡ እንኳ የአውሮፓ ህብረት የሰጠውን 217 ሚሊዮን ዩሮ ይህ ሳይጠና መሆን እንዳልነበረበት ተቃዋሚዎቹ የሚፈልጉት ነገር ቢኖር ሥልጣን ተቆርሶ እንዲሰጣቸው ሳይሆን የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴያቸው እንዳይገደብና እውነተኛ ምርጫ እንዲደረግ ምህዳሩ መስተካከል እንዳለበት አሳስበዋል፡፡ በአጠቃላይ ሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብት እንዲከበር ጫና እንዲያደርጉ፤ ኢህአዴግ ከተቃዋሚዎች ጋር እንዲደራደር እንዲያግባቡ የሚሉ ናቸው፡፡ አቶ ይልቃል ጌትነት በበኩላቸው ሁኔታው ወደ አስከፊ ደረጃ እያዘገመ በመሆኑና የኢህአዴግ ባህሪ ፍፁም አምባገነናዊ በመሆኑ ከንግዲህ ኢህአዴግ አጋር እንደማይሆናቸው ገልፀዋል፡፡ አቶ ልደቱ በበኩላቸው የኢትዮጵያ ዴሞክራሲ የታይታ (window dressing)፣ በህብረተሰቡ፣ በተቃዋሚዎችና በመንግስት በኩል ኋላ ቀር የፖለቲካ ባህል እንዳለ፣ ድህነት በበኩሉ የዴሞክራሲ ጠንቅ መሆኑ፣ ነፃ የዴሞክራሲ ተቋማት እንደሌሉና መንግስትና ፓርቲ እንደማይለዩ አስረድተዋል፡፡ ሰብሳቢዋ በበኩላቸው “COMPREHENSIVE SYSTEM OF DIALOGUE” እንዳላቸው፣ ጠ/ሚ/ሩን በአመት ሁለቴ እንደሚያገኟቸው፣ በፀረ ሽብር ህጉ ህገ ወጥነት እንደሚያምኑ፣ ለ2007ቱ ምርጫ ከወዲሁ ዝግጅት እንደጀመሩና የምርጫ ግብረኃይል እንዳቋቋሙ ገልጸዋል፡፡ አና ጎሜዝ በበኩላቸው ከኢትዮጵያኑ ባልተናነሰ የመንግስትን ባህሪያት ሲተነትኑ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ከዚህ ውይይት ብዙ ነገር እንደማይጠብቁ በማጠቃለያ ሀሳባቸው ገልጸውልናል፡፡
finote nesanet

No comments:

Post a Comment