Thursday, January 9, 2014

ምነው ከሲአይኤ (CIA) ጓሮ፣ ከወያኔ በራፍ በዚያ ትውልድ ላይ ጩኸት በረከተ?

ምነው ከሲአይኤ (CIA) ጓሮ፣ ከወያኔ በራፍ በዚያ ትውልድ ላይ ጩኸት በረከተ?!ከመላኩ ይስማው
በዚህ ሰሞን በኢትዮጵያዊነት ሰም ኢትዮጵያዊነትን ፈር የማሳት ጮኽት በርክቷል። በሀገር ታሪክ ተቆርቁዋሪነት ስም ታሪክን ማጥፋት። አንድን ትውልድ እንዳለ ኢትዮጵያዊነት የለሽ በማድረግ፣ ድልድይ በመስበር፣ የትግል ታሪክ ቅብብሎሽ እንዳይኖር ለማስቻል የታለመ ተንኮል።
በቀዘቃዛው ጦርነት ወቅትም ሆነ አሁን ከምእራቡ ዓለም አባዋራ ከአሜሪካ ጋር የተያያዘ የአገልጋይነት ሥራ እንዳለው፣ ወያኔ የጠና ችግር ውስጥ ሲገባ በሽማግሌነት ስም መውጫ ቀዳዳ በመፍጠር የሚታወቀው “ፕሮፌሰር” ኤፍሬም ይስሐቅ የ1960ዎቹን ያን ቀናዒ ኢትዮጵያዊ ትውልድ ታሪክ በቅጥረኛ ብዕሩ ሊያቆሽሽ ሞክሯል። ያለንበት ወቅታዊው የምዕራቡ ዓለም፡ የአፍሪካንም ሆነ የሌላውን ህዝብ ሀብት በነፃ ገበያ ስም ለማጋበስ እና ሐገሬውን የሸቀጣቸው ማራገፊያ ለማድረግ፣ በምርጫ ተደረገ ስም፣ የማስመስል ምርጫ አድርገው በሐገሬው ሕዝብ ላይ እንደ ወያኔ ዓይነት ምንደኛ እና ብሄራዊ ራዕይ የለሽ አጋሰስ ከሥልጣን መንበር ላይ ለማስቀመጥ፣ ይህም ካልተሳካ ብሄራዊ መግባባት እንዳይኖር በየሀገራቱ የፖለቲካ፣ የቋንቋ፣ የሃይማኖት ወዘተ ልዩነቶች መካከል መካረር እንዲኖር ተንኮል በመሥራት እርስ በርስ በማገዳደል፣ በምዕብ አፍሪካ፣ በመካከለኛው ምሥራቅ ወዘተ እንደታየው የተፈጥሮ ሃብት፣ የሰለጠነ የሰው ሃይል፣ ብሄራዊ ቅርሳ ቅርሶችን ለመዝረፍ፣ ለማዘረፍ በሚነዙት የኒዮ ሊበራሊዝም (ሰው በላ ካፒታሊዝም) ርዕዮተ ዓለም እስክስታ የሚወርደው “ጋዜጠኛው” እና በሙያው መስክ የልደቱ አያሌው ግልባጭ ተመስገን ደሳለኝም እንደዚያው የሚቆጠር ነው። (ይህ ዝርዝር ትችቱን ቀን ይጠብቅ )። በቅድሚያ እነኝህም ሆኑ ሌሎች “ያ ትውልድ ማርክሳዊ ሌሊናዊነትን የተከተለ ርዕዮተ ዓለም አምጥቶ ከኢትዮጵያዊነት ፈር ወጣ፣ ኢትዮጵያዊነትን ጎዳ”፣ የሚሉ የምዕራቡ ዓለም ፖለቲካ፣ ምጣኔ ሀብት እና ባህል አፍቃሪ ወይም ቅጥረኛ የሆኑ ፀሐፊዎች እና/ወይም ቀስቃሾች የሚያራግቡትን ክስ በገድል ማሚቶነት ከማራገባቸው በፊት፣ ቢያንስ የሚከተሉትን ነጥቦች ልብ ሊሉ የሚያስፈልግ ይመስለኛል
1. እራሳቸው በአሁኑ ወቅት የሚሰብኩት የኒዮ ሊብራሊዝም ይሁን የሰው በላ ካፒታሊዝም ወይም የመድብለ ፓርቲ ርዕዮተ ዓለም ከዘርዓያቆብ መፃሕፍት ወይም ከዋሸራው ኢትዮጵያዊ ትምህርት ቤት አልተቀዱም። የመጀመሪያው አሜሪካና እንግሊዝ በመሩት እና ብሬተን በተባለ ጉባኤ ላይ እ. ኤ. አ. በ1944 የተጠነሰሰ ሲሆን የሁለተኛው ቃል ሥርዎ መሰረት ግሪክ ነች። እንኳን በማህበራዊ፣ ፖለቲካዊና ምጣኔ ሀብታዊ ሳይንስ መስክ በጥቃቅን ነገሮችም ማህበረሰብ ከማህበረሰብ ይዋዋሳል። እናም የግራው ርዕዮተ ዓለም እንደ ማህበራዊ ሳይንስነቱ እያንዳንዱ ማህበረሰብ ከራሱ ጋር አስማምቶ ተግባር ላይ ሊያውላቸው የሚችል ትልቅ የሰዎች አእምሮ ውጤት ነው። ስለዚህም እነሱ ከጫፉ የማይደርሱት ያ ትውልድ በነበረበት ወቅት እና ሁኔታ ግራ ዘመም ቢሆን የሚያስወቅሰው ወንጀሉ አልገባኝም። ለነገሩ ከሳሾቹ ጥላቻ/ምንደኝነቱ አውሮዓቸው እንጅ፣ የሚያዳንቁት የምዕራብ አውሮፓም ከዚሁ ፍልስፍና ቀድቶ፣ ሥራ ላይ እያዋለው ያለውን የዌልፌር ሲስተም ቀደም ሲል ላቀረብኩት ተጠየቄ ማመሳከሪያ ነው።

2. እነሱም እራሳቸው በድርጊታቸው ወይም/ህይወታቸው ከብዙሃኑ ኢትዮጵያዊ የራቀ ታሪክ ያላቸው ሆነው ሳለ፣ ያን በህዝቡ ውስጥ ለህዝቡ ኖሮ ህይወቱን የገበረ ትውልድ ሾላ በድፍን ለመዝለፍ፣ ከመዝለፍም አልፎ ለመወንጀል የሞራል ብቃቱ የላቸውም። “ፕሮፌሰሩ” ከተሸከመው ማዕረግ ጀምሮ እስከ አለባበሱ ኑሮው ቢመረመር ከኢትዮጵያዊነት ይልቅ የባዕድ ቅጥረኛነቱን ያሳብቅበታል። በአባቱ ከየመን፣ በእናቱ ከኢትዮጵያ (ወለጋ) ነው በትውልዱ። እስከ ወያኔ አዲስ አበባ መግባት ድረስ የጂዊሸ ቆቡን ደፍቶ፣ በአሜሪካ ቅጥረኛነቱን ሲያካሂድ ቆይቶ፣ ከ1983 ጀምሮ ደግሞ ለበለጠ ማስመሰል ነጠላ ደረበ። ወያኔም አዲስ አበባ ሲገባ “አይኔ ታምር አየ” የሚልና ሌሎችን ግጥሞች ዘርፎ በኢትዮጵያዊነት ላይ ዘመተ፣ ወያኔ ሲያቅፈውም በስም ሽማግሌነት እና እርቅ በሚል ቀልድ በባህላችን ላይ ብቻ ሳይሆን በሀገራችን ላይ ተዛብተ፣ እየተዛበተም ነው – የ1997 ኡን ምርጫና የአስታራቂ ሽማግሌዎቹን ድራማ ያስታውሷል። በቅርቡም ይኸው ቀበሮ ፀረ-ኢትዮጵያዊ ፕሮፌሰር ወደ ኖርዌ ሄዶ፣ አፍቃሪ ኢትዮጵያ ሃይሎችን በማግለል፣ የተቀሩትን የግንጠላ ሀይሎችን አነጋግሮ ከወያኔ ጋር ለማስማማት መሞከሩ ይታወቃል። ቀደም ብሎም ወያኔ ገና ሥልጣን ላይ ከመውጣቱ በፊት ኢትዮጵያዊያን ሃይሎችን ለማሰባሰብ ቶሮንቶ ውስጥ በተካሄደው የመጀመሪያ ስብሰባ ላይ ተሳትፎ ወያኔ (ቲፒኤልፍ)፣ ሻዕቢያ (ኢፒኤልፍ) እና ኦነግ ካልተገኙ የትብብር ግንባር እንዳይመሰርቱ ሲከላከል እንደነበር ሀቅ ነው። የተባሉትንም ሆነ ሌሎች የኢትዮጵያ ጉዳይ የሚያገባቸውን ባለድርሻ አካላት በብዛት አግባብቶ በማምጣት በቀጣዩ ስብሰባ ግንባሩን ለመመስረት አዘጋጆች ሲሰየሙ አንዱ ሆኖ ተመርጦም እንደነበር ይታወቃል።
 በሰበብ አስባቡም ቀጣዩ ስብሰባ እንዳይካሄድ ሲያደናቅፍ ቆይቶ፣ በሌሎቹ አዘጋጆች ጉትጎታ ኢትዮጵያዊያን ሃይሎች ዳግመኛ ሲገናኙ፣ ይኸው እስስት ፕሮፌሰር እየጎተተ ይዞ የመጣው ላይፍ ኤንድ ፒስ የሚባል የስዊድን ተቁዋም ተወካዮችን ነበር። የፈረንጅ ተወካዮችን ማምጣት ብቻ ሳይሆን፣ እናንተ ለመተባበር ከመሞከር ይልቅ፣ በወቅቱ ወደ አዲስ አበባ እና አስመራ እየገሰገሱ ከነበሩት ከወያኔና ከሻዕቢያ ጋር ተስማምታችሁ ሥሩ የሚል እርኩስ ሃሳብ ነበር ያቀረበው። ለመሆኑ መለሰ ዜናዊን “ጓደኛዬና ታላቁ” ብሎ የሚያወድስ ህሊና ቢስ፣ እንዴት ነው ያን ክቡር ትውልድ ሊኮንን የሚችለው? ወገን! ፀረ-ኢትዮጵያ ጠላቶቻችን የትላንት ጀግኖቻችንን ታሪክ በመግደል፣ ዛሬ ምርኩዝ አልባ ሊያደርጉን እየጣሩ ነው ያለው። የቀረበልንን ሁሉ እየዋጥን ሀገራችንን ከማጥፋት እንጠንቀቅ።

በጋዜጠኛነት ስም ሌላው ልደቱ ሆኖ ህዝባዊ ትግሉን ለማደናቀፍ የተተከለውን፣ ሳይሞቅ ፈላ በተመለከተ ለወደፊቱ በሰፊው እመለስበታለሁ። ለዛሬው ግን ስለዚያ ትውልድ ለመፃፍ ብዕር ከማንሳቱ በፊት ቢያንስ ከዚህ በታች ያሉትን ታሪካዊ ፎቶዎች ልብ ብሎ እንዲያስተውል እመክረዋለሁ።ዛሬም ያልተመለሰው የሙስሊም ኢትዮጵያዊያን ጥያቄ ትላንትም ነበር ያ ትውልድ ትላንትም ስለ ሴቶች ተሳትፎ፣ ስለ ኑሮ ውድነት፣ ስለ ደመወዝ ዕድገትና ስለ ሌሎችም የብዙሃኑን ህይወት የሚመለከቱ ጉዳዮች ነበር የሚጠይቀ ሥራ ለሥራ ፈት! የድሃ ልጅ ይማር! የኢትዮጵያዊያን እስላሞች ችግር ለኢትዮጵያዊያን ነው! አንድነት ሃይል ነው! ነፃነት፣ እኩልነት፣ ወንድማማችነት! በኢትዮጵያ አንድነት ለዘላለም ይኑር! በሚሉ እና መሰል መፈክሮች አሰባሳቢነት ከመታገል በላይ ለዚያ ትውልድ ቀናዒ ኢትዮጵያዊነት ምን ማስረጃ ነው የሚፈለገው። የሃይማኖት እኩልነት ይከበር! የሚለውም የዚያ ትውልድ መፈክር ነበር።

3. የደንጊያ ሽበቱ ፕሮፌሰር፣ ለህዝባዊ ትግሉ በጭቃ እሾህነት የተተከለው “ጋዜጠኛ” ነኝ ባዩ ግለሰብ፣ ያን ትውልድ ከኢትዮጵያዊነት ራቀ ብለው ሲከሱ፣ ከዚህ በላይ ባሉት ፎቶዎች የሚታዩትንና ሌሎችንም መፈክሮች ይዞ በሰላማዊ መንገድ በመጠየቅ፣ ህይወቱን ከመስጠት፣ መከራ ከመቀበል በላይ ምን ዋጋ ሊከፍል እንደሚፈልጉ አይገባኝም። ዛሬም ያልተመለሱ፣ ተረካቢው ትውልድ ዛሬም ትግሉን የቀጠለባቸውን ጥያቄዎች ነበር ይዞ የተነሳው። ለዚህም በአምነስቲ ኢንተርናሽናል ግምት ክ500 000 በላይ ውድ የኢትዮጵያ ልጆች ወታደራዊው አገዛዝ ባወጀው የቀይ ሽብር ዘመቻ ብቻ የህይወት መስዋዕትነት ከፍለዋል። ቁጥራቸው የትየለሌ የሆነ ሌሎችም የአካልና የአእምሮ ስቃይ ተቀብለውበታል። ለመሆኑ መድብለ ፓርቲ የሚለውን ቃል ራሱ ኢሕአፓ አልነበረም ወደ ፖለቲካው መዝገበ ቃላት ያስገባው፤ ይህ ጥራዝ ነጠቅ “ጋዜጠኛ” ገና ፖለቲካ ምን መሆኑን ባላወቀበት ጊዜ?
ለዚህ ቆርጠው እንዲነሱ ያደረጋቸው በኢትዮጵያ የነበረው እውነታ፣ እንደ በላይ ዘለቀ፣ ታከለ ወልደሐወርያት፣ መንግሥቱ ንዋይ ወዘተ የመሳሰሉት ኢትዮጵያዊ ጀግኖች ራዕይ አንግበው የቀደዱት ፈር ነው። የትውልዱን የትግል አመለካከት የቀረፀው ሥርዓተ ትምህርቱ ብቻ አይደለም። በትምህርቱማ ቢሆን ከምዕራቡ ዓለም ተቀድቶ፣ በምዕራባዊያን መምህራን የተቀበለ ትውልድ ቀኝ ሳይሆን ግራ ዘመም ባልሆነ ነበር። ግራ ዘመምነቱ በፍፁም ኢትዮጵያዊነት እንደተገራም ደግሞ ያነሳቸው የመታገያ መፈክሮች ምስክር ናቸው። የትውልዱን አብዛኛ አባላት በጥላው ሥር አሰባስቦ ያታገለው ኢሕአፓም ቢሆን ገና ከመስራች ጉባዔው ጀምሮ ከሶሻሊስት ሀገሮች ጋር የሚያደርገው ግንኙነት በገለልተኛነት ላይ የተመሰረት እንዲሆን መወሰኑ፣ ግራ ዘመምነቱ የኢትዮጵያዊነት ራዕዩን እንዳያደበዝዘው ምን ያህል እንደታሰበበት የታሪክ ማስረጃ ነው።

በተቃራኒው ግን የዚያ ትውልድ ከሳሾች “ከሀገር ቤት ሳይቀዳ ከውጭ በመጣ ሥርዓተ-ትምህርት ውስጥ ስላለፈ፣ ኢትዮጵያን አያውቅም ነበር” የሚለውን ድፍን ክስ ሲሰነዝሩ ይገርሙኛል። በመጀመሪያ አሁን እነሱ ባህላዊ እያሉ የሚያወድሱት የቄስም ይሁን የመድረሳ ትምህርት ዱሮ ዱሮ መጤ ነበር – መካከለኛው ምሥራቅ ከጀመራቸው የክርስትናና የእስልምና ሃይማኖቶች= መጥቶ። በሁለተኛም ደረጃ እነሱም እንደየአቅማቸው ያለፉበት ትምህርት ያው ዓይነት ነው። አንዳንዶቹ ደግሞ ይብስ ከሀገር ርቀው፣ የትምህርት ክፍለ-ጊዜያቸውን ብቻ ሳይሆን ወራትን፣ አንዳንዴም ዓመታትን ከወገን ርቀው ያሳከፉና ለሀገራችን ባሕልም ባዕድ የሆኑ ነበሩ/ናቸውም ።

እስካሁን ያነሳሳሁዋቸውን እና የቀሩትን ተጠይቆዎች ያልመለሰ ድፍን ክስ መሰንዘሩ አሁን ለተያያዝነው ህዝባዊ ትግል ጠቀሜታው ምንድነው? የትላንቱን ለሀገሩ ቀናዒ ትውልድ ፍርሃትንና ግለኝነትን እምቢ ብሎ፣ ህዝባዊ ጥያቄዎችን አንስቶ ህይወቱን በሰጠ፤ የዛሬው ትውልድ በውሽት መነፀር እንዲመለከተው መጣሩ ለምንድነው? ያውም ገዳይንም ተገዳይንም በአንድ ላይ ጨፍልቆ፣ “ተጨራረሱ” በሚል አጉል ፈሊጥ። በሀገራችን አሁን ያለውን የወያኔ አገዛዝ እምቢ ብለው የተሰውት እነ ጋይም፣ ተስፋዬ፣ ሽብሬ፣ ወዘተ ወዘተ በነገው ትውልድ፣ አጓጉል ሞቱ ተብለው ታሪካቸው ሊወሳ ነው ማለት ነው? ምነው ከ ሲአይኤ ጓሮ፣ ከወያኔ በራፍ ጩኸት በረከተ? ዶሮ ሲጮኸ ሊነጋ ነው መሰል እንዲሉ ነውና ቀበቶ ጠበቅ አድርጎ፣ ጠላትን መትሮ ለይቶ ትግሉን ማፋፋም ነው ዘላቂ መፍትሄያችን። በሀገራችን 80 ዓመት እየደረሱ ያሉ አዛውንት “ፕሮፌሰሮች” (ይህ የሚወዱትና የሚጠሩበት ቃል ራሱ ባዕድ ነው!) ዛሬም ተባዕድ ቅጥረኞች ሆነው ትግላችንን እየጎዱ ናቸውና የኤፍሬሙ አያስደንቅም። የሀገራችን ጥቅስ ውሻ በበላበት ይጮ ሀል ይላል። ኤፍሬም ደግሞ የበላው ከባዕድ ማዕድ ነው፤ የሚውጠውም ወደነሱው ነው። የሚያደንቀው መሪ መለስ፤ የሚያሞግሰው ስርዓት የዘረኝነቱን ነው። ይህ ግለሰብ ነው ታዲያ ለሀገርና ለወገን የተሰዋውን ትውልድ ሀገሩን ካደ ብሎ ሊከስ የሚነሳው? ይልቁስ አቢዩ ጥያቄ ምነዋ አለቆቹ በዚያ ትውልድ ላይ ጨፍር ብለው ዛሬ አዘዙት የሚለው ነው።

No comments:

Post a Comment